ኢህአዴግ “የቀለም አብዮትና አመጽ የመምራት እድል አለው ያለውን የተማረውን የመንግስት ሰራተኛ ክፍል በፍጹም እንደማያምነው” ገለጸ

የካቲት ፲፯ (አስራ ሰባት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ኢህአዴግ ” የአገራችን ህዳሴና የሲቪል ሰርቪስ ሚና” በሚል ርዕስ ለከፍተኛ አመራሩ ስልጠና ባዘጋጀው ሰነድ ላይ፣ በመንግስት መስሪያ ቤት ውስጥ የሚገኘው የተማረው ክፍል በኢህአዴግ የመጨረሻው የማይታመነው ክፍል ነው ሲል ገልጾታል። “ይህ የተማረው ሃይል” ይላል ሰነዱ ” አመፅየመምራት፤ኢሳትና ቪኦኤን ከመሳሰሉ አፍራሽ ሚዲያዎች ጋር በመተባበር የቀለም አብዮት ለመምራት ፣ አመጽ ለማደራጀት እና መሪ ተዋናይ ለመሆን ያለው እድል ሰፊ ነው” ።
የተማረው የመንግስት ሰራተኛ “መንግስት ቢቀየር የኢህአዴግ ህልውና ቢንኮታኮት ግድ ” እንደማይሰጠው ሰነዱ ይጠቅስና፣ በምርጫ ድምጽ አሰጣጥም መርጦ ካልወጣ በስተቀር የማይታመን፣ በተጠራበት ሰልፍ የሚገኝ ” መሆኑን ይጠቅሳል።
በመንግስት መስሪያ ቤት  ውስጥ ያለው የተማረው ክፍል ህልውናውን ከኢህአዴግ ጋር መመስረት አለመቻሉን የሚገልጸው ሰነዱ፣ ምክንያቱ ደግሞ  “ከፍተኛ አመራሩ ፣ መካከለኛውና አባላቱም ጭምር፣ ሌላ መንግስት ቢመጣም በእውቀቱ እና በስራው መኖር እንደሚችል ማመኑ” ነው ይላል።
የተማረው የመንግስት ሰራተኛ “ለውጥ ፋላጊ ፣የመረጃ ሃይል እና አቅርቦት በተደራጀ አግባብ ያለው፣ እራሱን እንደሚዛናዊ ሃይል የሚቆጥር እና  በበደሉት ጥቂት አመራሮች ላይ አቂሞ የሚገኝ “እንዲሁም ሌላውንም የማስካድ አቅም ያለው በኢህአዴግ የመጨረሻው የማይታመነው ክፍል ነው ተብሎ በኢህአዴግ መፈረጁንም ሰነዱ ይገልጻል።
የመንግስት ሰራተኛው ልማታዊ አልሆነም የሚለው የስለጠና ሰነዱ፣ ይህንኑ ለመፈጸም በአምስት ክፍሎች የተዋቀረ የለውጥ ሰራዊት አደረጃጀት መዘጋጀቱንም ይናገራል። አንደኛው እና የለውጥ ሰራዊቱን የበላይ ሆኖ የሚቆጣጠረው ኮማንድ ፖስት የሚባለው ክፍል ሲሆን፣ በዚህ እዝ ስር ሚኒስትሮችና የተቋማት ስራ አስፈጻሚዎች መካተታቸውን ይናገራል። ሁለተኛው የስልጣን ክፍል ደግሞ ፕሮሰስ ካውንስል የሚባለው ሲሆን፣  በዚህ ከፍል የተቋም ሃላፊዎች ፣ የስራ ሂደት ሃላፊዎች ተመድበዋል። የስራ ሂደት በሚባለው ሶስተኛው ክፍል ደግሞ  የስራ ሂደት ሃላፊና የቡድን ሃላፊዎች ተካተውበታል። የቡድን ሰራተኞችን የያዘው አራተኛው ክፍል ፣ በስሩ ስለሚካተቱ ሰዎች አይዘረዝርም።  1 ለ5 ሰራተኞች የተባለው ደግሞ የመጨረሻው የአደረጃጀቱ ክፍሎች እና ታች ያለውን የመንግስት ሰራተኛ የሚመለከተው ነው።
የለውጥ ሰራዊቱ በዚህ መልኩ ተዋቅሮ እንደሚጓዝ ሰነዱ አስምሮበታል።
ኢህአዴግ የመንግስት ሰራተኛውን በራሱ መንገድ ለመቅረጽ የተጠቀመባቸው መንገዶች ሁሉ የተፈለገውን ውጤት እንዳላስገኙለት በሰነዱ ላይ ጠቅሶ፣ ቀጣዩ ስራ የለውጥ ሰራዊቱን  በዚህ መልኩ አደራጅቶ መጓዝ መሆኑንም አስቀምጧል።
የመንግስት ሰራተኛው ስለ አገሪቱ ህገ መንግስት፣ ስለ ህዝቦች ትግልና አገራዊ ህዳሴ እንዲሁም የልማታዊ ዲሞክራሲያዊ ስርአት ግንባታ ትግልና ፈተናዎች በቂ ግንዛቤ ካልያዘና ይህንንም በተጨባጭ በተግባር ማሳየት ካልቻለ ፣ ሚናውን ተወጥቷል ብሎ መናገር እንደማይቻል ሰነዱ ይጠቃሳል።http://ethsat.com/amharic/%E1%8A%A2%E1%88%85%E1%8A%A0%E1%8B%B4%E1%8C%8D-%E1%8B%A8%E1%89%80%E1%88%88%E1%88%9D-%E1%8A%A0%E1%89%A5%E1%8B%AE%E1%89%B5%E1%8A%93-%E1%8A%A0%E1%88%98%E1%8C%BD-%E1%8B%A8%E1%88%98%E1%88%9D%E1%88%AB/

 

Comments

Popular posts from this blog

Addis standard’s exclusive interview with Ana Gomes